ሃቃኒ ኔትወርክ (ኤችኪውኤን) በአፍጋኒስታን እና ፓኪስታን የሚንቀሳቀስ በ1970ዎቹ መጨረሻ የተመሠረተ ታጣቂ ድርጅት ነው፡፡ ኤችኪውኤን በዩናይትድ ስቴትስ እና በአፍጋኒስታን የጥምር ጦር አባላት ላይ በርካታ ከፍተኛ ጥቃቶች እና እገታ ፈጽሟል፡፡ በሰኔ 2004 ዓ.ም. በኮስት፣ አፍጋኒሰታን የአሜሪካ የጦር ካምፕ ላይ የተፈጸመው የአጥፍቶ ጠፊ ቦምብ ጥቃት ሁለት የአሜሪካ ወታደሮችን ሲገድል ከ100 በላይ የሆኑትን ደግሞ አቁስሏል፡፡ የአፍጋኒስታን ባለሥልጣናት በግንቦት 2009 ዓ.ም. ተፈጽሞ ከ150 በላይ ሰዎችን ለሞት የዳረገው በጭነት ተሽከርካሪ ላይ ለተጠመደ የቦምብ ፍንዳታ ፈጻሚው ሃቃኒ ኔትወርክ (ኤችኪውኤን) ነው ብለዋል፡፡ ሃቃኒ ኔትወርክ ከ100 በላይ ሰዎች የገደለው፣ በካቡል ለተፈጸመው በአምቡላንስ የተጠመደ ቦምብ ኃላፊነቱን ይወስዳል ተብሎ ይታመናል፡፡ እንዲሁም የአፍጋኒስታን ባለሥልጣናት በጥር 2010 ለተፈጸመው እና በካቡል በሚገኘው ዓለም ዓቀፍ ሆቴል ላይ ተፈጽሞ 22 ሰዎችን የገደለው ጥቃት ፈጻሚ ሃቃኒ ኔትወርክ ነው ብለዋል፡፡
በመስከረም 09 ቀን 2005 ዓ.ም. የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሃቃኒ ኔትወርክ (ኤችኪውኤን)ን በተሻሻለው የኢምግሬሽን እና ዜግነት ሕግ፣ በክፍል 219 መሠረት በውጭ አገር የሚገኝ ሽብርተኛ ድርጅት ብሎ ሰይሞታል፡፡ ቀደም ብሎ በመጋቢት 12 ቀን 2005 ዓ.ም. ደግሞ የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሃቃኒ ኔትወርክ ልዩ አለምአቀፍ ሽብርተኛ በማለት በስራ አስፈፃሚ ትእዛዝ (ኤክዘኪውቲቭ ኦርደር) 13224 እንደተሻሻለው መዝግቦታል፡፡ በዚህም መሰረት በዩናይትድ ስቴትስ አስተዳደር ወሰን ውስጥ የሚገኙ የሃቃኒ ኔትወርክ ንብረቶች እና ጥቅሞች ሁሉ ታግደዋል፣ ማናቸውም የዩናይትድ ስቴትስ ሰዎች ከሃቃኒ ኔትወርክ ጋር በምንም አይነት ልውውጥ ላይ መሳተፍ አይፈቀድላቸውም፡፡ በተጨማሪም በዩናይትድ ስቴትስ በውጭ አገር የሚገኝ ሽብርተኛ ድርጅት በሚል ለተመዘገበው ሃቃኒ ኔትወርክ ሆን ብሎ የማቴሪያል ወይም የሀብቶች አቅርቦት ማድረግ፣ ወይም ለማቅረብ መመሳጠር የተከለከለ ወንጀል ነው፡፡